ዲ.ዩ፤ ጥር 8/2016ዓ/ም (ህ.ዓ.ግ)፦ የዲላ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ጽሕፈት ቤት ከኢትዮጵያ ከኢንተርፕርነርሺፕ ልማት ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር በፐብሊክ ስራ ፈጠራና ተቋማዊ ለውጥ ዙሪያ ለዩኒቨርስቲው ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች ስልጠና መስጠቱ ተገልጿል።
ችሮታው አየለ (ዶ/ር )፣ የዲላ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት፤ በስልጠናው መዝጊያ መርሃግብር ላይ ባደረጉት ንግግር፤ ስልጠናው አሳታፊና በተግባር የተደገፈ፣ የግልም ይሁኑ የተቋም ችግሮች በቀላሉ በመለየት ወደ ዕድል በመቀየር ለውጦችን ለማምጣት እንድንችል ግንዛቤና መነቃቃትን የሚያሳድር ስልጠና ነበር ሲሉ ገልጸዋል። ፕሬዝዳንቱ አያይዘውም፤ የተፈጠረውን ግንዛቤና መነቃቃት ወደ ተግባር ለመቀየር ኮሌጆች፣ ዳይሬክቶሬቶች እና የስራ ክፍሎች እንዲሁም የሚመለከተው አካል ሁሉ በተቋሙ የሚታዩ ችግሮችን በፍጥነት በመለየት ወደ ለውጥ ትግበራ ለመግባት ርብርብ እንዲያደርግ አሳስበዋል።
አቶ መሳይ ፍቅሩ፣ የዲላ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ጽሕፈት ቤት ሀላፊ በበኩላቸው፤ በዩኒቨርስቲው የተልዕኮ ልየታን፣ ራስ ገዝነትንና ሌሎች በመንግሥትና በተቋሙ እየተሰሩ ያሉ የለውጥ ስራዎችን ስኬታማ ለማድረግ ታስቦ የተዘጋጀ ስልጠና መሆኑን ጠቅሰው፤ ሰልጣኞች በራሳቸው የሚተማመኑ፤ ጠንካራ ተነሳሽነት ያላቸው፤ ኃላፊነታቸውን በአግባቡ የሚወጡ፤ ለለውጥ ዝግጁ የሆኑና ጠንካራ ፍላጎትና አላማን ይዘው ስኬት ለማስመዝገብ ፅናት ያላቸው እንዲሆኑ የሚያግዝ እና የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና እንደሆነ ገልጸዋል።
አቶ ቴዎድሮስ አበበ፣ በኢንተርፕርነርሺፕ ልማት ኢንስቲትዩት (EDI) የስልጠና ከፍተኛ ባለሙያ፤ ስልጠናው የተቋሙ መሪዎች ራሳቸውን ለስራ ፈጠራና ለተቋማዊ ለውጥ ዝግጁ በማድረግ ያላቸውን የሰው ኃይልና ውሱን በጀት በመጠቀም በተቋሙ ያሉ ተግዳሮቶችን ወደ ዕድል በመቀየር ተቋሙ ራሱን ችሎ እንዲቆምና በስሩ የሚገኙ ሰራተኞችን ኑሮ ማሻሻል እንዲችል መንገድ የሚያሳይ የግንዛቤ ማስጨበጫና ማነቃቂያ ስልጠና መሆኑን ተናግረዋል።
አቶ ይመኑ ዳካ፣ የዩኒቨርስቲው ተቋማዊ ለውጥ ጽሕፈት ቤት ዳይሬክተር፣ ስልጠናውን መሳተፋቸው ለራሳቸውና ለተቋማቸው የሚጠቅም እና ችግሮችን በመለየት እንዴት ወደ ዕድል መቀየር እንደሚቻል ግንዛቤ ያዳበሩበት እንደነበር ገልጸዋል።
መሰል ስልጠናዎች ለታችኛው አመራርና ለፈፃሚ ሰራተኛ በቀጣይ እንደሚዘጋጁ ለማወቅ ተችሏል።
የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት
ዲላ ዩኒቨርሲቲ









