ዲ.ዩ፤ የካቲት 11/2016 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፦ በአገር አቀፍ ደረጃ ለሁለተኛ ጊዜ ከየካቲት 06 -11/2016 ዓ.ም ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የመጀመሪያ ዲግሪ ተመራቂ ተማሪዎች ሲሰጥ የነበረው የመውጫ ፈተና ዛሬ ተጠናቋል።
ዲላ ዩኒቨርሲቲ ትምህርት ሚኒስቴር ባወጣው መርሃ ግብር መሰረት 393 የዲላ ዩኒቨርሲቲ መደበኛ ተመራቂዎች፣ 457 የግል ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እጩ ተመራቂዎች፣ እንዲሁም በ2015 ዓ.ም የመውጫ ፈተና ተፈትነው ዘንድሮ ዳግም የሚፈተኑ 210 የሚደርሱ ተማሪዎች፤ በአጠቃላይ ከ1000 ለሚበልጡ እጩ ምሩቃን ፈተናውን ሰጥቷል።
ችሮታው አየለ (ዶ/ር )፣ የዲላ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት፤ የኢፌድሪ ትምህርት ሚኒስቴር ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች የመውጫ ፈተና በአመት ሁለት ጊዜ እንዲሰጥ በሚል ያስተላለፈውን መመሪያ ተከትሎ ዩኒቨርሲቲው ሰፊ ቅድመ ዝግጅቶች ሲደረግበት በመቆየቱ ከየካቲት 6/2016 ዓ.ም ጀምሮ ለስድስት ተከታታይ ቀናት ሲሰጥ የቆየው የመውጫ ፈተና በሰላም መጠናቀቁን ገልጸዋል።
ዶ/ር ችሮታው አክለውም፤ ዩኒቨርሲቲው ባለፈው አመት በተሰጠው የመውጫ ፈተና ጥሩ ውጤት ማስመዝገቡን አስታውሰው፤ ዘንድሮም በሁሉም ትምህርት ክፍሎች በሚሰጡ የመውጫ ፈተናዎች እንደ ተቋም ይህን ውጤት በተሻለ ሁኔታ ለማስቀጠል ለተማሪዎቹ ቲቶሪያሎችን ጨምሮ የተለያዩ ሞዴል ፈተናዎችን በተደጋጋሚ በመስጠት ተመራቂዎቹ ተገቢውን የስነ ልቦና ዝግጅት እንዲያደርጉ ሲሰራ መቆየቱን ተናግረዋል።
ፈተናው በሰላም እንዲጠናቀቅ ሰፊ አበርክቶ ለነበራቸው የፈተናውን ግብረ ኃይል ጨምሮ የዞን የፀጥታ ዘርፍ፣ የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ እና መካከለኛ አመራሮች፣ መምህራንና የአስተዳደር ዘርፍ ሰራተኞች እንዲሁም የአይ.ሲ.ቲ ዳይሬክቶሬት ከነሙሉ አባላቱ እንዲሁም ለሁሉም ባለድርሻ አካላት ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
ፈተናቸውን አጠናቀው ሲወጡ ያገኘናቸው ተመራቂ ተማሪዎቹ አቶ ደመላሽ ደበበ እና አቶ ኤፍሬም በቀለ፤ ፈተናው በጥሩ ሁኔታ መጠናቀቁ እንዳስደሰታቸው ገልጸው፤ አሁን ላይ እንደ ሀገር ለቅድመ ምሩቃን ተመራቂዎች የመውጫ ፈተና መጀመሩ በሀገሪቱ ጥራት ያለው ትምህርት ለማስቀጠል ትልቅ ሚና እንደሚኖረው ተናግረዋል።
ዲላ፤
የአረንጓዴው ምድር ዩኒቨርሲቲ
የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት
FB: https://www.facebook.com/Du.edu.et
Telegram:https://t.me/dprd9
website: https://www.du.edu.et
Email: https://www.pirdir@du.edu.et



