ዲ.ዩ፤ ጥር 07/2016 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፦ የዲላ ዩኒቨርሲቲ ትምህርት ጥራት ማሻሻያ ዳይሬክቶሬት እና አካዳሚክ ፕሮግራሞች ዳይሬክቶሬት በጋራ ለተመራቂ ተማሪዎች በሚሰጠው የመውጫ ፈተና ሞዴል ፈተና አዘገጃጀት ዙሪያ ለመምህራን ስልጠና ሰጥተዋል።
አቶ ዮናስ ተጠምቀ፣ የዲላ ዩኒቨርሲቲ አካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት ጽ/ቤት ኃላፊ ፤ እንደ አገር በትምህርት ዘርፍ የተሻለ ዜጋን ለማፍራት የመውጫ ፈተና አስፈላጊነት ከፍተኛ እንደሆነ አስረድተው ተማሪዎች በተቋም ደረጃ የሚሰጠውን ፈተና ማለፍ ከቻሉ ለምን የአገር አቀፍ መውጫ ፈተናን ይወድቃሉ በሚል የተዘጋጀ ስልጠና መሆኑን ገልጸዋል።
አቶ ዮናስ አክለውም፤ ይህ ስልጠና ወጥ የሆነ የፈተና አዘገጃጀትና ብቃት ያለውን ትውልድ ለማፍራት ብሎም ተማሪዎችም ሆኑ መምህራን የመውጫ ፈተናውን ከሀገር አቀፍ የመውጫ ፈተና ጋር ተመሳሳይ ለማድረግና በርካታ ተማሪዎችን ለማሳለፍ የዚህ ስልጠና ሚና የጎላ እንደሆነም ተናግረዋል፡፡
ዶ/ር በቀለ መንገሻ፣ የዲላ ዩኒቨርሲቲ ትምህርት ጥራትና ማሻሻያ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር በበኩላቸው፤ የትምህርት አላማዎችን ስኬት በመፍጠር የትምህርት ጥራትና የአካዳሚክ ብቃትን ለማረጋገጥ የትምህርት ምዘና አይነተኛ መሳሪያ መሆኑ ገልጸዋል።
የመውጫ ፈተና የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ እና ሀገሪቱ የምትፈልገውን የሰለጠነ የሰው ሀይል ለማፍራት የማጽፈፀሚያ ስልት እንደሆነም ጭምር አያይዘው ገልጸዋል።
በመውጫ ፈተና ተማሪዎችን አብቅቶ ማሳለፍ ተቋማችንን በተማሪዎች ዘንድ ተመራጭ ለማድረግ እንደሚረዳ ገልጸው፤ በያዝነው 2016 የትምህርት ዓመት አጋማሽ እና በዓመቱ የመጨረሻ አካባቢ ለሚመረቁ ተማሪዎች የመውጫ ፈተና (Exit Exam) ውጤታማነት ከፍተኛ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ስልጠናውን ሲከታተሉ ካገኘናቸው መምህራን መካከል መምህር ብርሃኑ በቀለ፣ የማኔጅመንት ትምህርት ክፍል መምህር እና መምህርት አበባ ለታ፣ የግብርናና ተፈጥሮ ሀብት ኮሌጅ መምህርት በበኩላቸው፤ ይህ ስልጠና ለመምህራን መሰጠቱ እንደ አገር ወጥ የሆነ ፈተና ለማዘጋጀት እንደሚረዳ ገልጸው፤ የተማሪዎች ውጤታማነት ለተማሪዎች ስኬት ከመሆንም ባለፈ የመምህራን እርካታ የሚፈጥር መሆኑን ገልጸውልናል።
የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት




