ዲ.ዩ፤ ጥር 26/2016 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፦ የዲላ ዩኒቨርሲቲ ስቴም ማዕከል በ2016 ዓ.ም በቅዳሜ እና እሁድ መርሐ ግብር የሚያስተምራቸውን አዲስ ተማሪዎች ተቀብሎ የእንኳን ደህና መጣችሁ መርሃ ግብር አካሂዷል።
በመርሃ ግብሩ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የዲላ ዩኒቨርሲቲ የኢንዱስትሪ ግንኙነትና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዳይሬክተር አዲሱ ፍሪንጆ (ዶ /ር)፤ የስቴም ማዕከሉ በቅዳሜ እና እሁድ መርሃ ግብር አዲስ ለሚገቡ ተማሪዎች አቀባበል በማድረግ በ2016 ዓ.ም በሀገር አቀፍ ደረጃ በተደረገው የስቴም ውድድር አሸናፊ ለነበሩ 25 ተወዳዳሪዎች የእውቅና ስርተፍኬት መስጠቱን ገልጸው፤ ለአዲስ ተማሪዎች የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ዶ/ር አዲሱ አክለውም፤ ማዕከሉ የቆፌ እና የዲላ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን ጨምሮ ዲላ ከተማ ውስጥ ከሚገኙ ስድስት የ2ኛ ደረጃ ት/ቤቶች የተወጣጡ 120 ተማሪዎችን ተቀብሎ በቅዳሜ እና እሁድ መርሃ ግብር በማሰልጠን ተማሪዎች በሳይንስ እና ቴክኖሎጂ መስኮች ያላቸውን ዕውቀት በተግባር በተደገፈ መልኩ እንዲያዳብሩ በማድረግ በሀገሪቷ ቀጣይ ስራ ፈጣሪ ትውልድ ለመፍጠር እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
አቶ በፈቃዱ ተድላ፣ የዲላ ዩኒቨርሲቲ ስቴም ማዕከል ዳይሬክተር በበኩላቸው፤ ፕሮግራሙ በዋናነት አዲስ ገቢ ተማሪዎችን ከአሁን በፊት በማዕከሉ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን ሲሰሩ ከነበሩ ሲንየር ተማሪዎች ጋር ልምድ ልውውጥ እንዲያደርጉ ለማስቻል ታስቦ የተዘጋጀ ፕሮግራም እንደሆነ ተናግረዋል።
በፕሮግራሙ ላይ ንግግር ያደረጉት የጌዴኦ ዞን ሳይንስና ቴክኖሎጂ ጽ/ቤት የስራ ፈጠራና ድጋፍ አገልግሎት ባለሙያ አቶ ትግሉ በቀለ፤ ጽ/ቤታቸው አሁን ላይ ከዲላ ዩኒቨርሲቲ ጋር ከፍተኛ የሆነ የስራ ግንኙነት በመፍጠር በቅርበት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸው፤ በስቴም ማዕከሉ ላለፉት አራት አመታት ከዞኑ ትምህርት መምሪያ ጋር በመቀናጀት በክረምት እንዲሁም በቅዳሜ እና እሁድ መርሃ ግብሮች ከ500 መቶ በላይ ተማሪዎችን ማሰልጠን መቻሉን ተናግረዋል።
በመርሃ ግብሩ ላይ ተገኝተው ልምዳቸውን ሲያካፍሉ ካገኘናቸው ተማሪዎች መካከል ተማሪ ቤዛዊት ፍቃዱ እና ተማሪ ምንተስኖት አሳየ፤ ማዕከሉ ተማሪዎች ቀደም ሲል ከመምህራን በንድፈ ሃሳብ የቀሰሙትን ዕውቀት በተግባር ጭምር በመማር የቴክኖሎጂ ዕወቀትን በበቂ ሁኔታ እንዲያገኙ የሚያስችል ስለሆነ አሁን ላይ ማዕከሉ በተማሪዎች ዘንድ ትልቅ መነቃቃትን እየፈጠረ እንደሚገኝ ገልጸውልናል።
በሳምንቱ የእረፍት ቀናት መርሐ ግብር በዲላ ዩኒቨርሲቲ የስቴም ማዕከል የሚሰለጥኑ 120 ተማሪዎች እስከ ሰኔ መጨረሻ ድረስ ስልጠናውን የሚወስዱ መሆኑን ከአዘጋጆቹ ተገልጿል።








