ዲ.ዩ፤ ነሐሴ 11/2016 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፦ የዲላ ዩኒቨርሲቲ ህክምና እና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ጠቅላላ ሆስፒታል “በጎነት ለጤናችን” በሚል መሪ ቃል ከነሐሴ 10-20/2016 ዓ.ም ድረስ የሚቆይ የክረምት በጎ ፍቃድ ነፃ የጤና ምርመራ እና ህክምና አገልግሎት በዲላ ከተማ በተመረጡ ቦታዎች እየሰጠ ይገኛል።
ዶክተር ሀይሌ ተስፋዬ ፣ በዲላ ዩኒቨርሲቲ የጤናና ህክምና ሳይንስ ኮሌጅ አጠቃላይ ሆስፒታል የህክምናና ተግባር ስልጠና ዋና ዳይሬክተር እንደገለጹት፤ ይህ የክረምት በጎ ፍቃድ ነፃ የጤና አገልግሎት ዘመቻ ጤና ሚኒስቴር በሀገር አቀፍ ደረጃ ለሁለት ሚሊዮን ዜጎች በክረምት በጎ ፍቃድ የነፃ ምርመራና ህክምና አገልግሎት ለመስጠት አቅዶ ለየጤና ተቋማቱ ባከፋፈለው ኮታ መሰረት የዲላ ዩኒቨርሲቲ አጠቃላይ ሆስፒታል እስከ 11 ሺህ 500 ለሚደርሱ ገንዘብ ከፍለው አገልግሎትን ለማግኘት አቅም የሌላቸው የዲላ ከተማ እና አካባቢ ነዋሪዎች ተደራሽ ለማድረግ ያለመ መሆኑን ተናግረዋል።
ይህ የበጎ ፍቃድ ነፃ የህክምና አገልግሎት የሁሉንም ባለድርሻ አካላት ርብርብ የሚፈልግ ስራ እንደመሆኑ በበጎ ፍቃድ ዘመቻው ከከተማው አስተዳደርና ከዞኑ ጤና መምሪያ አንስቶ ብዙዎችን አሳታፊ ለማድረግ ጥሪዎች እንደተደረጉ ገልጸው፤ በዚህም የከተማው ቀይ መስቀል እና ደም ባንክ አገልግሎት ጥሪውን በይፋ ተቀብለው አብረው እየሰሩ እንደሚገኙ በመግለፅ፤ በቀጣይ ሌሎች አካላትም በተመሳሳይ ነፃ የጤና አገልግሎት ዘመቻው እንደሚቀላቀሉ እምነታቸው መሆኑን ዶ/ር ሀይሌ አያይዘው ተናግረዋል።
ዶ/ር ሀይሌ አክለውም፤ ለ10 ቀናት በከተማው በተመረጡ ቦታዎች ማለትም በቆፌ ሚችሌ ጀግኖች አደባባይ እና በዲላ ከተማ ማዞሪያ ላይ በተዘጋጁ ጊዜያዊ የህክምና ጣቢያዎች በሚሰጡ የነጻ ህክምና አገልግሎቶች በተለይ የስኳር መጠን፣ ደም ግፊት፣ ስነ-ምግብ ልኬት፣ የቆዳ እና አባላዘር እንዲሁም የቲቢ (ሳምባ ነቀርሳ) የመሳሰሉ በሽታዎች ህክምና አገልግሎት በትኩረት እንደሚሰጥ ገልጸው፤ ምናልባት በህክምናው ወቅት ተጨማሪ ህክምና የሚያስፈልጋቸው ካሉም ወደ ሆስፒታሉ በመላክ ህክምና እንደሚሰጣቸው ተናግረዋል።
አያይዘውም ማህበረሰቡ በነቂስ ወጥቶ የዚህን የክረምት የበጎ ፍቃድ የጤና አገልግሎት ተጠቃሚ እንዲሆን ዶ/ር ሀይሌ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።
የጤና ህክምና አገልግሎቱን ሲጠቀሙ ያገኘናቸው አስተያየት ሰጪዎች እንደገለጹልን፤ የዚህ አይነቱ የነፃ ህክምና አገልግሎት ከክረምት ባለፈ በተለያዩ ጊዚያትም ጭምር ቢሰጥ በከተማው ከፍለው መታከም ለማይችሉ የማህበረሰብ ክፍሎች ትልቅ እገዛ እንደሚያደርግ አንስተዋል።
በበጎ ፍቃድ አገልግሎቱ ከነፃ ምርመራና ህክምና በተጨማሪ የደም ልገሳ መርሃ ግብር እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ ገልጸዋል።
ዲላ፤
የአረንጓዴው ምድር ዩኒቨርሲቲ
የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት
FB: https://www.facebook.com/Du.edu.et
Telegram:https://t.me/dprd9
website: https://www.du.edu.et
Email: https://www.pirdir@du.edu.et