ዲላ ዩኒቨርሲቲ
ዲ.ዩ ታህሳስ 12/2016 ዓ.ም (ህ.ዓ.ግ)፦ የዲላ ዩኒቨርሲቲ አጠቃላይ ሆስፒታል ለይርጋጨፌ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል በስፔሻሊስት ሀኪሞች አማካኝነት ሙያዊ ድጋፍ በማድረግ ላይ መሆኑ ተገልጿል።
አቶ ትዛአለኝ ተስፋዬ፣ የዲላ ዩኒቨርሲቲ የጤናና ህክምና ሳይንስ ኮሌጅና አጠቃላይ ሆስፒታል ዋና ስራ አስፈጻሚ እንደገለጹት፤ የህክምና ሙያ ድንበር የማይገድበው በመሆኑ የዲላ አጠቃላይ ሆስፒታል የጤና ባለሙያዎች በይርጋጨፌ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል የእናቶችን ሞት ለመቀነስ እየሰሩ ናቸው።
አቶ ትዝአለኝ አክለውም፣ በ2015 ዓ.ም በተደረገው ጥናትና ክትትል የእናቶችን ሞት በተመለከተ ከ7ቱ 5ቱ ከይርጋጨፌ ሪፈር ተብለው የመጡ እንደነበር በመረዳት የእነዚህን እናቶች ሞትና ችግር ለመቅረፍ በቅርበት መስራት ስለሚያስፈል ሆስፒታሉ የህክምና ድጋፍ እያደረገ መሆኑን አስረድተዋል።
በሳምንት ሁለት ቀን በስፔሻሊስት ሐኪሞች እየተሰጠ ያለው ሙያዊ ድጋፍ በቀዶ ጥገና፣ በህጻናት፣ በውስጥ ደዌ፣ በማህጸን እና ጽንስ ህክምና ዙሪያ መሆኑን አቶ ትዛለኝ ተናግረዋል፡፡
ዶ/ር አማኑኤል ደንሳ፣ የጠቅላላ ቀዶ ህክምና ስፔሻሊስት የኮሚኒቲ ሰርቪስ አስተባባሪ በበኩላቸው፤ በገንዘብ እጦትና በቦታ ርቀት የሚቸገሩ የማህበረሰብ ክፍሎችን ለመታደግ ታስቦ እየተሰራ መሆኑን ገልፀው፤ አሁን ላይ በይርጋጨፌ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ላይ እየተደረገ ያለው ድጋፍ እንግልትንና ሞትን ለመቀነስ የሚኖረው ሚና የጎላ መሆኑን አስገንዝበዋል።
ዶ/ር አማኑኤል አክለውም፤ በይርጋጨፌ የሚሰጠው ህክምና በዲላ አጠቃላይ ሆስፒታል ላይ የሚኖረውን የስራ ጫና በመቀነስና በቀላሉ እዚሁ ለመፍታት የሚቻሉ ችግሮች በቦታው በመፍታት ትልቅ እገዛ አለው ብለዋል፡፡
ዶ/ር በኃይሉ ተሾመ፣ የይርጋጨፌ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር፤ በበኩላቸው ይህ ድጋፍ ለህብረተሰቡ ከሚሰጠው ጠቀሜታ ባለፈ ለሙያተኞች የስራ ጫናን የመቀንስ፣ ከፍ ሲልም የልምድ ልውውጥ የሚደረግበትና ከፍተኛ ክህሎት የሚገኝበት ነው ብለዋል፡፡
አቶ ተካልኝ አያነው፣ የይርጋጨፌ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ተወካይ ስራ አስፈጻሚ፤ የዲላ ዩኒቨርሲቲ ጤናና ህክምና ሳይንስ ኮሌጅ አጠቃላይ ሆስፒታል በአሁኑ ሰዓት በይርጋጨፌ ሆስፒታል እጥረት የተስተዋለባቸውን የመብራት፣ የውሃና የተለያዩ ግብዓቶችን በማሟላት እያደረገ ላለው እገዛ አመስግነው፤ ይህ ድጋፍ ቀጣይነት እንዲኖረው ጠይቀዋል።
ቀዶ ህክምና ተደርጎላቸው ያገኘናቸው አርሶ አደር አክሊሉ ባት፣ ለረጅም ግዜ በዕባጭ ሲቸገሩ እንደቆዩና ሌላ ቦታ ሄደው ለመታከም የአቅም ችግር እንደነበረባቸው ገልጸው፤ የዲላ አጠቃላይ ሆስፒታል በይርጋጨፌ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል በሳምንት ለሁለት ቀናት በሚሰጠው የስፔሻሊስቶች ህክም ተጠቃሚ በመሆን ካጋጠማቸው የጤና እክል ፈውስ ማግኘታቸውን ገልጸዋል፤ አያይዘውም ላገኙት ድጋፍ አመስግነዋል።
የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት
የአረንጓዴው ምድር ዩኒቨርሲቲ
Telegram: https://t.me/dprd9
Email: pirdir@du.edu.et